የከተማ የውሃ አቅርቦት ጥናትና ዲዛይን መመዘኛና መለኪያ ጋይድ ላይን ላይ ምክክር ተደረገ፡፡
መጋቢት 2015 ዓ.ም (ው.ኢ.ሚ) የከተማ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ጥናትና ዲዛይን መመዘኛና መለኪያ ጋይድ ላይን ዙሪያ ምክክር ተካሄደ።
የምክክር መድረኩን በንግግር የከፈቱት የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ የምክክር መድረኩ አላማ በቀረበው ረቂቅ ሰነድ (ጋይድላይን) ላይ ለመወያየት እና በግብዓት እንዲዳብር ያለመ መሆኑን ገልጸው፤ የከተማ ውሃ አቅርቦት ጥናትና ዲዛይን ጋይድላይን መዘጋጀቱ ለዜጎች የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ላይ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት እንደሚያግዝ ገልጸው፤ የውሃ አቅርቦት ሽፋን በማስፋፋት ደረጃውን የጠበቀ እና ንጽህናው የተረጋገጠ የውሃ አቅርቦት ለህብረተሰቡ ለማዳረስ የከተማ ውሃ አቅርቦት ጥናትና የዲዛይንና መመዘኛ እና መለኪያ ጋይድላይን ችግር ፈቺ እንደሚሆን ጠቁመዋል፡፡
የመርሃግብሩ አስተባባሪና በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የመጠጥ ውሃ አቅርቦት መሪ ስራ አስፈጻሚ አቶ ታምሩ ገደፋ በበኩላቸው የከተሞች ውሃ አቅርቦት ጥናትና ዲዛይን መለኪያ ጋይድላይን ቀደም ብሎ የተጀመረ ቢሆነም በአሁኑ ጊዜ በዘርፉ እየታዩ ያሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ግምት ውስጥ ያስገባ የመጠጥ ውሃ ስታንዳርድ እና መመዘኛ ጋይድ ላየን ማዘጋጀት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው፤ ጥናቱን በሚያካሂዱት አማካሪ ድርጅቶች በኩል የመጀመሪያ ሪፖርት ቀርቦ ተገምግሞ ወደ ቀጣይ ስራዎች እንደሚገባ አመላክተዋል ፡፡
አማካሪ ድርጅቶቹ በውሃ አቅርቦት ጥናት ዲዛይን መመዘኛና መለኪያ ጋይድላይን ዙሪያ ጥናቶችን በማቅረብ ከተሳታፊዎች አስተያየት እና ሀሳቦችን ተቀብለዋል፡፡
በመድረኩ የውሃና ኢነርጂ ሚንስቴር የበላይ አመራሮች፣ የፌደራል እና ክልሎች መንግሥታዊና የግል ድርጅት ተወካዮች፣ ኮንትራክተሮችና አማካሪዎች ተሳትፈውበታል ፡፡